
ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን በኢትዮጵያ የቻይና አምባሳደር ጋር ተወያዩ፡፡
ባሕር ዳር፡ ጥር 06/2013 ዓ.ም (አብመድ) ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አቶ ደመቀ መኮንን በኢትዮጵያ የቻይና አምባሳደር ጃው ጂዩዋንን በቢሮአቸው ተቀብለው አነጋግረዋል።
በውይይታቸው ከተነሱት ዋና ዋና ጉዳዮች መካከል የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ፣ የኢትዮጵያ ታላቁ ህዳሴ ግድብ እና ወቅታዊ የትግራይ ክልል ሁኔታ በተለይ ደግሞ በክልሉ ያሉ አዳዲስ ክስተቶችን በሚመለከት ፍሬያማ ውይይት አካሂደዋል፡፡
በውይይቱ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አቶ ደመቀ የጃክ ማ ፋውንዴሽንን ጨምሮ የቻይና መንግስት እና ኩባንያዎች ዓለም አቀፉን ወረርሽኙን ለመዋጋት ላደረጉት ከፍተኛ ድጋፍ አድናቆታቸውን ገልፀዋል፡፡
ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ “በአፍሪካ ለሚፈጠሩ ችግሮች አፍሪካዊ መፍትሄዎች” የሚለውን መርህ ያስተጋባውን ቻይና የህዳሴ ግድብ ድርድርን በተመለከተ የምትከተለው በመርህ ላይ የተመሠረተን አቋም አድንቀዋል፡፡
ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ደመቀ በቅርቡ በትግራይ ክልል ስለተፈጠሩ ክስተቶች በሰጡት ማብራሪያ መንግሥት በክልሉ የሕግ የበላይነትን ማስጠበቅ ዘመቻ አድርጎ በስኬት ማጠናቀቁንና ከዓለምአቀፍ ምግባረ ሰናይ ተቋማት ጋር የሰብዓዊ እርዳታ ማድረስ ሥራ በጋራ ጥረት መቀጠሉን ገልፀዋል፡፡ በክልሉም የትህነግ ቡድን ያፈራረሳቸው መሰረተ ልማቶችን መልሶ የመገንባት ሥራ እየተከናወነ እንደሚገኝ አመላክተዋል፡፡
የትህነግ መሪዎችን በቁጥጥር ስር የማዋል ሥራ ተጠናክሮ መቀጠሉንና ክልሉም ወደ መደበኛ ሁኔታ እየተመለሰ መሆኑን አቶ ደመቀ ተናግረዋል፡፡
አምባሳደር ጃው ጂዩዋን በበኩላቸው በኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ አስቸጋሪ ጊዜያት ውስጥ ኢትዮጵያ ከቻይና ጋር በአጋርነት በመቆሟ የመንግስታቸውን ምስጋና እና አድናቆት ገልፀዋል፡፡
ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በሀገሪቱ ወሳኝ ጉዳዮች ላይ ላደረጉላቸው ገለፃ ምስጋናቸውን ያቀረቡት አምባሳደሩ፤ በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለውን ጠንካራ ግንኙነት ለማሳደግ እንደሚሰሩ ቃል መግባታቸውን ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል ዐቀባይ ጽሕፈት ቤት የተገኘ መረጃ ያመላክታል፡፡
ተጨማሪ መረጃዎችን ከአብመድ የተለያዩ የመረጃ መረቦች ቀጣዮቹን ሊንኮች በመጫን ማግኘት ትችላላችሁ፡፡
The post ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን በኢትዮጵያ የቻይና አምባሳደር ጋር ተወያዩ፡፡ appeared first on Satenaw Ethiopian News/Breaking News.