
በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን የባሕርዳር ሀገረ ስብከት ለመተከል ተፈናቃዮች ድጋፍ አደረገ።
ባሕር ዳር፡ ጥር 7/2013 ዓ.ም (አብመድ) በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን የባሕርዳር ሀገረ ስብከት ለመተከል ዞን ተፈናቃዮች ከ1ነጥብ1 ሚሊዮን ብር በላይ የሚያወጡ ልዩ ልዩ ሰብዓዊ ድጋፎችን አደረገ፡፡

ድጋፉን በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን የባሕር ዳር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል በብጹዕ አቡነ አብርሐም የተመራ ልዑክ በቻግኒ ከተማ አቅራቢያ በሚገኘው የተፈናቃዮች መጠለያ ጣቢያ በአካል ተገኝቶ አስረክቧል፡፡
በድጋፍ ርክክብ ስነ ስርዓቱ ላይ ብፁእ አቡነ አብርሐም ቤተ ክርስትያን ችግሩ እንዲቃለል ለፈጣሪ ከምታደርሰው ፀሎትና ልመና ባሻገር ምእመናን ተረዳድተውና ተደጋግፈው ይህን አስከፊ ጊዜ እንዲያልፉ ጥሪዋን እያቀረበች መሆኑን ተናግረዋል፡፡
ብፁነታቸው ለተፈናቃዮቹ ችግሩን በፅናት እንዲሻገሩትም አባታዊ ምክርና ቡራኬ ለግሰዋል፡፡
ድጋፉን የተረከቡት የአማራ ክልል አደጋ መከላከልና ምግብ ዋስትና ፕሮግራምና ልዩ ድጋፍ የሚሹ አካባቢዎች ማስተባበሪያ ኮሚሽን የቅድመ ማስጠንቀቂያና ፈጣን ምላሽ ማስተባበሪያ ዳይሬክተር አቶ ጀምበሩ ደሴ ለጋሾች ለተፈናቃዮች የሚያደርጉት ሰብዓዊ ድጋፍ ተጠናክሮ መቀጠሉን ተናግረዋል፡፡

የተሰበሰቡ ድጋፎችን ለተፈናቃዮች በፍትሐዊነት በማዳረስ ሊደርስ የሚችለውን ሰብዓዊ ቀውስ ለመቀነስ በትኩረት እየተሰራ መሆኑንም አቶ ጀምበሩ ገልፀዋል፡፡
ተፈናቃዮች በበኩላቸው ህብረተሰቡ እያደረገ ላለው ሰብዓዊ ድጋፍ ምስጋናቸውን በማቅረብ በድጋፍ ስርጭቱ ላይ የሚስተዋሉ ችግሮች መፈታት እንዳለባቸው ተናግረዋል፡፡
በአማራ ክልል ከሚገኙ ከ270 ሺህ በላይ ተፈናቃዮች ውስጥ ከ61 ሺህ በላይ የሚሆኑት በአዊ ብሔረሰብ አስተዳደር በሚገኙ መጠሊያ ጣቢያዎች እንደሚገኙም ከኮሚሽኑ የተገኘው መረጃ ያመላክታል፡፡
ዘጋቢ:– ሳሙኤል አማረ
ተጨማሪ መረጃዎችን ከአብመድ የተለያዩ የመረጃ መረቦች ቀጣዮቹን ሊንኮች በመጫን ማግኘት ትችላላችሁ፡፡
The post በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን የባሕርዳር ሀገረ ስብከት ለመተከል ተፈናቃዮች ድጋፍ አደረገ። appeared first on Satenaw Ethiopian News/Breaking News.